Tuesday 26 May 2015

« በጉልበት ወደ ዘመናዊነት »

የኢትዮጵያ ምርጫ እና የጀርመን የዘገባ ሽፋን
እሁድ በመላው ኢትዮጵያ የተካሄደውን 5ኛ ሀገር አቀፍ ምርጫ ለመታዘብ የአውሮፓ ህብረት ልዑካን ወደ ኢትዮጵያ ባይሄዱም ፤ የዶይቸ ቬለን ሬዲዮ እና ቴሌቪዥንን ጨምሮ የጀርመን ጋዜጦች ስለምርጫው ዘግበዋል። የጥቂቱን የጀርመን ጋዜጦች ዘገባ እንደሚከተለው ነበር።
የጀርመን ታዋቂ ዕለታዊ ጋዜጣ « ዙድ ዶይቸ ሳይቱንግ» ስለ የኢትዮጵያ ሀገር አቀፋዊ ምርጫ ሲዘግብ ርዕሱን« በጉልበት ወደ ዘመናዊነት » ነው ያለው። የጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ ፓርቲ ኢሀዲግ እንደሚያሸንፍ ጥርጥር የለውም ሲል የዘገበው ይህ ጋዜጣ ፤ «ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በርግጥ ጥሩ የኢኮኖሚ እድገት ያስመዘገበች ሀገር ብትሆንም አሁንም ድረስ እንደ « ልማታዊ አምባገነን» ነው የምትታየው፣ መንግሥት የኤኮኖሚውን አቅጣጫ ብቻ ሳይሆን ህብረተሰቡንም ይቆጣጠራል ሲልም አትቷል ።ጋዜጣው የሰብዓዊ መብት ተማጋች ድርጅቶችን ዋቢ በማድረግ፤ ሂስ ሰንዛሪ ጋዜጠኞች በሀገሪቱ ቦታ እንደሌላቸው ወህኒ ቤት የሚገኙ ጋዜጠኞችን እና የኢንተርኔት ዘጋቢዎችን በምሳሌነት ጠቅሶ ያብራራል። ጋዜጣው ስለ ሃገሪቱ ልማትም ፅፏል። ምንም እንኳን ልማቱ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ማህበረሰበብ ጋር ባይደርስም፤ በአዲስ አበባ ትላልቅ ፎቆች እየተሰሩ ስለመሆኑና በቅርቡ የቀላል ባቡር አገልግሎት ስራውን እንደሚጀምር ይጠቁማል።
« ዙድ ዶይቸሳይቱንግ»የኢትዮጵያ ምርጫ ሀተታውን ከማጠናቀቁ በፊትም፤ የተቃዋሚዎች እጣ ፋንታ ከባለፈው ምርጫ ጋር ሲነፃፀር አለመሻሻሉንም አንስቷል። እንደ ጋዜጣው ቀውስ ውስጥ ከሚገኙት ከሶማሊያ እና ከደቡብ ሱዳን ጋር ስትነፃፀር ምዕራባውያን ኢትዮጵያን የተረጋጋች ደሴት አድርገው ስለሚመለከቷት የዲሞክራሲ ርዕስ ሲነሳ ፤ ጆሮ ደባ ልበስ ብለው ያልፉታል።
ሌላው ስለ ኢትዮጵያ ምርጫ የዘገበው «ታገስሻው» የተባለው የጀርመን የዜና ማሰራጫ ነው። «ተቃዋሚ ድምፅ የለውም» በሚለው ርዕሱ፤ የምርጫው አሸናፊ ፓርቲ ኢሀአዲግ እንደሚሆን እንደማያጠራጥር ያትታል። ታገስሻው ከዚህም በተጨማሪ ፤ በቴሌቪዥን ሥርጭቱ እና በድረ ገጹ ከሀገር ሸሽቶ ናይሮቢ ውስጥ ጥገኝነት ስለጠየቀው ጋዜጠኛ የትነበርክ እና ደረሰብኝ ስለሚለው በደል ዘግቧል።
«ፍራንክፈርተር አልገማይነር » የተባለው የጀርመን ጋዜጣም ቢሆን እንደሌሎቹ ጋዜጦች ፤ማን ምርጫውን እንደሚያሸንፍ ግልፅ ነው ይላል፤ « እንደ ብረት የጠጠረ አገዛዝ ባላት ሀገር» በሚለው ርዕሱ ከ457 የምክር ቤት መቀመጫ 456ቱን ኢሀአዲግ ይዞ የመራው ሀገር እንደሆነ በመግለፅ፣ ጋዜጣው ፤ የተቃዋሚዎችን ነፃ አለመሆን እና ብሶት ያትታል። ከዚህም በተጨማሪ ጋዜጣው ፤ ምናልባትም ነፃ ምርጫ ታይቶበታል ያለውን የ97ቱን ምርጫ እና ከዛም በኋላ ስለተነሳው አመፅ እና በወቅቱም ከ200 በላይ ሰዎች ስለመሞታቸው አውስቷል። ከዚህም በተጨማሪ የኢትዮጵያ መንግሥት ፣ አሸባሪ ቡድናትን በመዋጋት የዩናይትድ ስቴትስ ስልታዊ አጋር መሆኑን ጋዜጣው ጠቅሷል ።

No comments:

Post a Comment